bible
ra
🌐 Language
English
Español
Français
Deutsch
Português
Italiano
Nederlands
Русский
中文
日本語
한국어
العربية
Türkçe
Tiếng Việt
ไทย
Indonesia
All Languages
Home
/
Amharic
/
Amharic NASV (አዲሱ መደበኛ ትርጒም)
/
Proverbs 8
Proverbs 8
Amharic NASV (አዲሱ መደበኛ ትርጒም)
1
ጥበብ ጮኻ አትጣራምን? ማስተዋልስ ድምፅዋን ከፍ አድርጋ አታሰማምን?
2
በመንገድ አጠገብ ባሉ ኰረብቶች፣ መንገዶቹ በሚገናኙበትም ላይ ትቆማለች፤
3
ወደ ከተማዪቱ በሚያስገቡት በሮች አጠገብ፣ በመግቢያዎቹ ላይ፣ ድምፅዋን ከፍ አድርጋ እንዲህ ስትል ትጮኻለች፤
4
“ሰዎች ሆይ፤ የምጠራው እኮ እናንተን ነው፤ ለሰው ልጆች ሁሉ ድምፄን ከፍ አደርጋለሁ።
5
እናንተ ብስለት የጐደላችሁ፤ ጠንቃቃነትን ገንዘብ አድርጉ፤ እናንተ ተላሎች፤ ማስተዋልን አትርፉ።
6
የምናገረው ጠቃሚ ነገር ስላለኝ አድምጡኝ፤ ቀና ነገር ለመናገር ከንፈሮቼን እከፍታለሁ።
7
አንደበቴ እውነትን ይናገራል፤ ከንፈሮቼ ክፋትን ይጸየፋሉና።
8
ከአንደበቴ የሚወጡት ቃሎች ሁሉ ጽድቅ ናቸው፤ አንዳቸውም ጠማማና ግራ የሚያጋቡ አይደሉም።
9
በጥልቅ ለሚያስተውሉ ሁሉም ቀና ናቸው፤ ዕውቀት ላላቸውም ስሕተት የለባቸውም።
10
ከብር ይልቅ ምክሬን፣ ከንጹሕ ወርቅ ይልቅ ዕውቀትን ምረጡ፤
11
ጥበብ ከቀይ ዕንይበልጥ ውድ ናትና፤ ከምትመኙት ነገር ሁሉ አንዳች የሚስተካከላት የለም።
12
“እኔ ጥበብ ከማስተዋል ጋር አብሬ እኖራለሁ፤ ዕውቀትና ልባምነት ገንዘቦቼ ናቸው።
13
እግዚአብሔርን መፍራት ክፋትን መጥላት ነው፤ እኔም ትዕቢትንና እብሪትን፣ ክፉ ጠባይንና ጠማማ ንግግርን እጠላለሁ።
14
ምክርና ትክክለኛ ፍርድ የእኔ ናቸው፤ ማስተዋል አለኝ፤ ብርታት አለኝ።
15
ነገሥታት በእኔ ይነግሣሉ፤ ገዦችም ትክክል የሆነውን ሕግ ይደነግጋሉ፤
16
መሳፍንት በእኔ ይገዛሉ፤ በምድር ላይ የሚገዙ መኳንንትም ሁሉ በእኔ ያስተዳድራሉ።
17
የሚወድዱኝን እወድዳቸዋለሁ፤ ተግተው የሚሹኝም ያገኙኛል።
18
ሀብትና ክብር፣ ዘላቂ ብልጽግናና ስኬት በእኔ ዘንድ አሉ።
19
ፍሬዬ ከንጹሕ ወርቅ ይበልጣል፤ ስጦታዬም ከነጠረ ብር።
20
እኔ በጽድቅ መንገድ እሄዳለሁ፤ በፍትሕም ጐዳና እጓዛለሁ፤
21
ለሚወድዱኝ ብልጽግና እሰጣለሁ፤ ግምጃ ቤታቸውንም እሞላለሁ።
22
“ እግዚአብሔር ከቀድሞ ሥራዎቹ በፊት፣ የተግባሮቹ መጀመሪያ አድርጎ አመጣኝ፤
23
ዓለም ከመፈጠሩ አስቀድሞ፣ ከጥንት ከዘላለም ተሾምሁ።
24
ከውቅያኖሶች በፊት፣ የውሃ ምንጮች ከመፍለቃቸው በፊት ተወለድሁ፤
25
ተራሮች ገና ሳይመሠረቱ፣ ከኰረብቶችም በፊት ተወለድሁ፤
26
ምድርን ወይም ሜዳዎቿን፣ ወይም ምንም ዐይነት የዓለም ትቢያን ከመፍጠሩ በፊት እኔ ተወለድሁ።
27
ሰማያትን በዘረጋ ጊዜ፣ በውቅያኖስ ላይ የአድማስ ምልክት ባደረገ ጊዜ እኔ እዚያ ነበርሁ፤
28
ደመናትን በላይ ባጸና ጊዜ፣ የውቅያኖስን ምንጮች በመሠረተ ጊዜ፣
29
ለባሕር ድንበርን በከለለ ጊዜ፣ ውሆችም የእርሱን ትእዛዝ እንዳያልፉ፣ የምድርንም መሠረቶች ወሰን ባበጀ ጊዜ፣
30
በዚያን ጊዜ ከጐኑ ዋና ባለሙያ ነበርሁ። ሁልጊዜ በፊቱ ሐሤት እያደረግሁ፣ ዕለት ተዕለት በደስታ እሞላ ነበር፤
31
የእርሱ በሆነው መላው ዓለም ሐሤት እያደረግሁ፣ በሰው ልጆች ደስ እሰኝ ነበር።
32
“እንግዲህ፣ ልጆቼ ሆይ፤ አድምጡኝ፤ መንገዴን የሚጠብቁ ቡሩካን ናቸው።
33
ምክሬን አድምጡ፤ ጥበበኞች ሁኑ፤ ቸልም አትበሉት።
34
በየዕለቱ ደጃፌ ላይ የሚጠብቅ፣ በበራፌ ላይ የሚጠባበቅ፣ የሚያዳምጠኝ ሰው ቡሩክ ነው።
35
የሚያገኘኝ ሁሉ ሕይወትን ያገኛልና፤ ከእግዚአብሔርም ዘንድ ሞገስን ይቀበላል።
36
የሚያጣኝ ሁሉ ግን ራሱ ይጐዳል፤ የሚጠሉኝም ሁሉ ሞትን ይወድዳሉ።”
← Chapter 7
Chapter 9 →