bible
ra
🌐 Language
English
Español
Français
Deutsch
Português
Italiano
Nederlands
Русский
中文
日本語
한국어
العربية
Türkçe
Tiếng Việt
ไทย
Indonesia
All Languages
Home
/
Amharic
/
Amharic NASV (አዲሱ መደበኛ ትርጒም)
/
Proverbs 27
Proverbs 27
Amharic NASV (አዲሱ መደበኛ ትርጒም)
1
ነገ በሚሆነው አትመካ፤ ቀን የሚያመጣውን አታውቅምና።
2
ሌላው ያመስግንህ እንጂ የገዛ አፍህ አይደለም፤ ሌላ ሰው ያወድስህ እንጂ የገዛ ከንፈርህ አይሁን።
3
ድንጋይ ይከብዳል፤ አሸዋም ሸክም ነው፤ የተላላ ሰው ጕነጣ ግን ከሁለቱም ይከብዳል።
4
ንዴት ጨካኝ፣ ቍጣም ጐርፍ ነው፤ በቅናት ፊት ግን ማን መቆም ይችላል?
5
የተገለጠ ዘለፋ፣ ከተደበቀ ፍቅር ይሻላል።
6
ከጠላት ደጋግሞ መሳም ይልቅ፣ የወዳጅ ማቍሰል ይታመናል።
7
ለጠገበ ማር አይጥመውም፤ ለተራበ ግን እሬት እንኳ ይጣፍጠዋል።
8
ከቤቱ ወጥቶ የሚባዝን ሰው፣ ጎጆዋን ለቅቃ እንደምትባዝን ወፍ ነው።
9
ሽቱና ዕጣን ልብን ደስ ያሰኛሉ፤ የወዳጅ ማስደሰትም ከቅን ምክሩ ይመነጫል።
10
የራስህንም ሆነ የአባትህን ወዳጅ አትተው፤ መከራ በሚያጋጥምህ ጊዜ ወደ ወንድምህ ቤት አትሂድ፤ ሩቅ ካለ ወንድም ቅርብ ያለ ጎረቤት ይሻላል።
11
ልጄ ሆይ፤ ጠቢብ ሁን፤ ልቤን ደስ አሰኘው፤ ለሚንቁኝ ሁሉ መልስ መስጠት እችል ዘንድ።
12
ጥንቁቅ አደጋን አይቶ ይሸሸጋል፤ ማስተዋል የጐደለው ግን ወደዚያው ይሄዳል፤ ይጐዳልም።
13
ለማይታወቅ ሰው የተዋሰን ልብሱን ግፈፈው፤ ለዘልዛላ ሴት ከተዋሰማ ዐግተው።
14
ሰው ድምፁን ከፍ አድርጎ ባልንጀራውን በማለዳ ቢመርቅ፣ እንደ ርግማን ይቈጠራል።
15
ጨቅጫቃ ሚስት፣ በዝናብ ቀን እንደሚወርድ የማያቋርጥ ጠፈጠፍ ናት፤
16
እርሷን ለመግታት መሞከር፣ ነፋስን እንደ መግታት ወይም ዘይትን በእጅ እንደ መጨበጥ ነው።
17
ብረት ብረትን እንደሚስል፣ ሰውም ሌላውን ሰው እንደዚሁ ይስለዋል።
18
በለስን የሚንከባከብ ፍሬዋን ይበላል፤ ጌታውን የሚያገለግልም ክብርን ይጐናጸፋል።
19
ውሃ ፊትን እንደሚያሳይ፣ የሰውም ልብ ማንነቱን ገልጦ ያሳያል።
20
ሲኦልና የሙታን ዓለም እንደማይጠግቡ ሁሉ፣ የሰውም ዐይን አይረካም።
21
ብር በማቅለጫ፣ ወርቅ በከውር እንደሚፈተን፣ ሰውም በሚቀበለው ምስጋና ይፈተናል።
22
ጅልን በሙቀጫ ብትወቅጠው፣ እንደ እህልም በዘነዘና ብታደቅቀው፣ ጅልነቱን ልታስወግድለት አትችልም።
23
በጎችህ በምን ሁኔታ እንዳሉ ደኅና አድርገህ ዕወቅ፤ መንጋህንም ተንከባከብ፤
24
ሀብት ለዘላለም አይኖርምና፤ ዘውድም ከትውልድ ወደ ትውልድ ጸንቶ አይኖርም።
25
ደረቁ ሣር ተወግዶ፣ አዲሱ ብቅ ሲል፣ በየኰረብታው ላይ ያለው ሣር ተሰብስቦ ሲገባ፣
26
ከበግ ጠቦቶች ልብስ ታገኛለህ፤ ፍየሎችም የዕርሻ መሬት መግዣ ይሆኑሃል።
27
አንተንና ቤተ ሰብህን፣ ገረዶችህንም ጭምር ለመመገብ፣ የተትረፈረፈ የፍየል ወተት ይኖርሃል።
← Chapter 26
Chapter 28 →