bible
ra
🌐 Language
English
Español
Français
Deutsch
Português
Italiano
Nederlands
Русский
中文
日本語
한국어
العربية
Türkçe
Tiếng Việt
ไทย
Indonesia
All Languages
Home
/
Amharic
/
Amharic NASV (አዲሱ መደበኛ ትርጒም)
/
Isaiah 44
Isaiah 44
Amharic NASV (አዲሱ መደበኛ ትርጒም)
1
“ነገር ግን አሁንም ባሪያዬ ያዕቆብ፣ የመረጥሁህ እስራኤል ሆይ፣ ስማ፤
2
የፈጠረህ፣ በማሕፀን የሠራህ፣ የሚረዳህ፣ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ባሪያዬ ያዕቆብ፣ የመረጥሁህ ይሹሩን ሆይ፣ አትፍራ።
3
በተጠማ ምድር ላይ ውሃ፤ በደረቅ መሬት ላይ ወንዞችን አፈስሳለሁና፤ መንፈሴን በዘርህ፣ በረከቴንም በልጅ ልጅህ ላይ አወርዳለሁ።
4
እነርሱም በለመለመ መስክ ላይ እንደ ሣር፣ በወንዝ ዳር እንደ አኻያ ዛፍ ይበቅላሉ።
5
አንዱ፣ ‘እኔ የእግዚአብሔር ነኝ’ ይላል፤ ሌላው ራሱን በያዕቆብ ስም ይጠራል፤ ሌላው ደግሞ በእጁ ላይ ‘ የእግዚአብሔር ነኝ’ ብሎ ይጽፋል፤ ራሱን በእስራኤል ስም ይጠራል።
6
“የእስራኤል ንጉሥና ቤዛ እግዚአብሔር ፣ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ የፊተኛውም እኔ ነኝ፤ የኋለኛውም እኔ ነኝ፤ ከእኔ በቀር ሌላ አምላክ የለም።
7
እስቲ እንደ እኔ ማን አለ? ይናገር፤ ሕዝቤን ከጥንት ስመሠርት ምን እንደ ነበረ፣ ገና ወደ ፊት ምን እንደሚሆን፣ ይናገር፤ በፊቴ ያስረዳ፤ ስለሚመጣውም ነገር አስቀድሞ ይናገር።
8
አትፍሩ፤ አትደንግጡ፤ ይህን አልነገርኋችሁምን? ቀድሞስ አላሳወቅኋችሁምን? ለዚህ እናንተ ምስክሮቼ ናችሁ። ከእኔ በቀር ሌላ አምላክ አለን? ፈጽሞ! ወይም ሌላ ዐለት አለ? የለም! ማንንም አላውቅም።”
9
ጣዖት የሚሠሩ ሁሉ ከንቱዎች፣ የሚሠሩባቸውም ነገሮች ዋጋ ቢስ ናቸው፤ የሚናገሩላቸው ዕውሮች ናቸው፤ ዕውቀት የላቸውም ያፍራሉም።
10
ለምንም የማይጠቅመውን አምላክ የሚቀርጽ፣ ጣዖትን የሚያበጅስ ማነው?
11
ጣዖት የሚሠራ ሰው እንጂ ሌላ አይደለም፤ እርሱና መሰሎቹም ያፍራሉ፤ ሁሉም ተሰብስበው በአንድ ላይ ይቁሙ፤ ይደነግጣሉ፤ ይዋረዳሉም።
12
ብረት ቀጥቃጭ መሥሪያን ይይዛል፤ በከሰል ፍም ላይ ይሠራዋል፤ ጣዖትን በመዶሻ ቅርጽ ይሰጠዋል፤ በክንዱም ኀይል ያበጀዋል። ከዚያም ይራባል፤ ጕልበት ያጣል፤ ውሃ ይጠማል፤ ይደክማል።
13
ጠራቢ በገመድ ይለካል፤ በጠመኔ ንድፍ ያወጣል፤ በመሮ ይቀርጸዋል፤ በጸርከል ምልክት ያደርግበታል። በሰው አምሳል ይቀርጸዋል፤ የሰውንም ውበት ያለብሰዋል፤ በማምለኪያም ስፍራ ያስቀምጠዋል።
14
ዝግባ ይቈርጣል፤ ሾላ ወይም ዋንዛ ይመርጣል፤ በደን ውስጥ ካሉት ዛፎች ጋር እንዲያድግ ይተወዋል፤ ወይም ጥድን ይተክላል፤ ያንንም ዝናም ያሳድገዋል።
15
ሰው ለማገዶ ይጠቀምበታል፤ ከዚያም ጥቂት ወስዶ በማንደድ ይሞቀዋል፤ እንጀራም ይጋግርበታል። ከዚሁ ጠርቦ አምላክ ያበጃል፤ ያመልከዋል፤ ጣዖትን ይሠራል፤ ወድቆም ይሰግድለታል።
16
ግማሹን ዕንጨት ያነድደዋል፤ በላዩ ምግቡን ያበስልበታል፤ ሥጋ ጠብሶበት እስኪጠግብ ይበላል፤ እሳቱን እየሞቀ እንዲህ ይላል፤ “ዕሠይ ሞቀኝ፤ እሳቱም ይታየኛል።”
17
በቀረው ዕንጨት የጣዖት አምላኩን ይሠራበታል፤ ወድቆ ይሰግድለታል፤ ያመልከዋል፤ ወደ እርሱም እየጸለየ፣ “አንተ አምላኬ ነህ፤ አድነኝ” ይላል።
18
ምንም አያውቁም፤ አያስተውሉም፤ እንዳያዩ ዐይናቸው ተሸፍኗል፤ እንዳያስተውሉ ልባቸው ተዘግቷል።
19
ማንም ቆም ብሎ አላሰበም፤ ዕውቀት ወይም ማስተዋል ስለሌለው እንዲህ ማለት አልቻለም፤ “ግማሹን በእሳት አቃጥዬዋለሁ፤ በፍሙ እንጀራ ጋግሬበታለሁ፤ ሥጋ ጠብሼበት በልቻለሁ፤ ታዲያ፣ በቀረው እንዴት ጸያፍ ነገር እሠራለሁ? ለግንድስ መስገድ ይገባኛልን?”
20
ዐመድ ይቅማል፤ ተታላይ ልብ አስቶታል፤ ራሱን ለማዳን አይችልም፤ “ይህ በቀኝ እጄ ያለው ነገር ሐሰት አይደለምን?” ለማለት አልቻለም።
21
“እስራኤል ሆይ፤ ባሪያዬ ነህና፣ ያዕቆብ ሆይ፤ ይህን ዐስብ። እኔ ሠርቼሃለሁ፤ አንተም ባሪያዬ ነህ፤ እስራኤል ሆይ፤ አልረሳህም።
22
መተላለፍህን እንደ ደመና፣ ኀጢአትህን እንደ ማለዳ ጭጋግ ጠርጌ አስወግጃለሁ፤ ተቤዥቼሃለሁና ወደ እኔ ተመለስ።”
23
ሰማያት ሆይ፤ እግዚአብሔር ይህን አድርጓልና ዘምሩ፤ የምድር ጥልቆች ሆይ፤ በደስታ ጩኹ። እናንት ተራሮች፣ እናንት ደኖችና ዛፎቻችሁ ሁሉ እልል በሉ፤ እግዚአብሔር ያዕቆብን ተቤዥቷል፣ በእስራኤልም ክብሩን ገልጧልና።
24
“ከማሕፀን የሠራህ፣ የተቤዠህም፣ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ “ሁሉን ነገር የፈጠርሁ፣ ብቻዬን ሰማያትን የዘረጋሁ፣ ምድርን ያንጣለልሁ፣ እኔ እግዚአብሔር ነኝ።
25
የሐሰተኞችን ነቢያት ምልክቶች አከሽፋለሁ፤ ሟርተኞችን አነሆልላለሁ፤ የጥበበኞችን ጥበብ እገለባብጣለሁ፤ ዕውቀታቸውንም ከንቱ አደርጋለሁ።
26
የባሪያዎቼን ቃል እፈጽማለሁ፤ የመልእክተኞቼን ምክር አጸናለሁ። “ኢየሩሳሌምን ‘የሰው መኖሪያ ትሆኛለሽ’፣ የይሁዳ ከተሞችንም፣ ‘ይታነጻሉ’፣ ፍርስራሻቸውን፣ ‘አድሳለሁ’ እላለሁ።
27
ጥልቁን ውሃ፣ ‘ደረቅ ሁን፤ ወንዞችህን አደርቃለሁ’ እላለሁ።
28
ቂሮስንም፣ ‘እርሱ እረኛዬ ነው፤ ፈቃዴን ሁሉ ይፈጽማል፤ ኢየሩሳሌምም፣ “እንደ ገና ትሠራ”፣ ቤተ መቅደሱም፣ “መሠረቱ ይጣል” ይላል’ እላለሁ።”
← Chapter 43
Chapter 45 →