bible
ra
🌐 Language
English
Español
Français
Deutsch
Português
Italiano
Nederlands
Русский
中文
日本語
한국어
العربية
Türkçe
Tiếng Việt
ไทย
Indonesia
All Languages
Home
/
Amharic
/
Amharic NASV (አዲሱ መደበኛ ትርጒም)
/
Isaiah 37
Isaiah 37
Amharic NASV (አዲሱ መደበኛ ትርጒም)
1
ንጉሡ ሕዝቅያስ ይህን ሲሰማ፣ ልብሱን ቀደደ፤ ማቅ ለበሰ፤ ወደ እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ገባ።
2
የቤተ መንግሥቱን አስተዳዳሪ ኤልያቄምንና ጸሓፊውን ሳምናስን እንዲሁም ከካህናቱ ዋና ዋናዎቹን ማቅ ለብሰው ሁሉም ወደ አሞጽ ልጅ ወደ ነቢዩ ኢሳይያስ እንዲሄዱ ላካቸው።
3
እነርሱም እንዲህ አሉት፤ “ሕዝቅያስ እንዲህ ይላል፤ ‘ይህ ቀን የጭንቀት፣ የተግሣጽና የውርደት ቀን ነው፤ ሕፃናት ሊወለዱ ሲሉ ብርታት እንደሚታጣበት ቀን ሆኗል።
4
ሕያው አምላክን ይገዳደር ዘንድ ጌታው የአሦር ንጉሥ የላከውን የጦር አዛዡን ቃል እግዚአብሔር አምላክህ ይሰማ ይሆናል፤ እግዚአብሔር አምላክህም ሰምቶ ይገሥጸው ይሆናል፤ ስለዚህ አንተም በሕይወት ለተረፉት ቅሬታዎች ጸልይ።’ ”
5
የንጉሡ የሕዝቅያስ መልእክተኞች ወደ ኢሳይያስ መጡ፤
6
ኢሳይያስም እንዲህ አላቸው፤ “ጌታችሁን እንዲህ በሉት፤ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ‘የአሦር ንጉሥ ባሪያዎች እኔን ስለ ሰደቡኝ፣ በሰማኸው ቃል አትሸበር።
7
እነሆ፤ በላዩ መንፈስን እሰድዳለሁ፤ ወሬም ሰምቶ ወደ አገሩ ይመለሳል፤ በገዛ አገሩም በሰይፍ እንዲወድቅ አደርጋለሁ።’ ”
8
የጦር አዛዡም፣ የአሦር ንጉሥ ለኪሶን ለቅቆ መሄዱን ሲሰማ፣ ከነበረበት ተመለሰ፤ ንጉሡም የልብናን ከተማ ሲወጋ አገኘው።
9
ደግሞም ሰናክሬም፣ የኢትዮጵያ ንጉሥ ቲርሐቅ ሊወጋው መምጣቱን ሰማ፤ ይህንም እንደ ሰማ ወደ ሕዝቅያስ መልእክተኞች ላከ፤ እንዲህም አለ፤
10
“ለይሁዳ ንጉሥ ለሕዝቅያስ እንዲህ በሉት፤ ‘ኢየሩሳሌም በአሦር ንጉሥ አትያዝም’ ብሎ የተማመንህበት አምላክ አያታልልህ።
11
እነሆ፤ የአሦር ነገሥታት በአገሮች ሁሉ ላይ ያደረጉትን፣ ፈጽሞም እንዳጠፏቸው ሰምተሃል፤ አንተስ የምታመልጥ ይመስልሃልን?
12
የቀደሙት አባቶቼ ያጠፏቸውን፣ የጎዛንን፣ የካራንን፣ የራፊስን እንዲሁም በተላሳር የሚኖሩ የዔድንን ሰዎች የአሕዛብ አማልክት አድነዋቸዋልን?
13
የሐማት ንጉሥ፣ የአርፋድ ንጉሥ፣ የሴፈርዋይም ከተማ ንጉሥ፣ የሄና ንጉሥ ወይም የዒዋ ንጉሥ የት አሉ?”
14
ሕዝቅያስ ደብዳቤውን ከመልእክተኞቹ ተቀብሎ አነበበው፤ ወደ እግዚአብሔር ቤተ መቅደስ ወጥቶም ደብዳቤውን በእግዚአብሔር ፊት ዘረጋው።
15
ሕዝቅያስም እንዲህ ሲል ወደ እግዚአብሔር ጸለየ፤
16
“በኪሩቤል ላይ የምትቀመጥ፣ የእስራኤል አምላክ፣ የሰራዊት ጌታ እግዚአብሔር ሆይ፤ በምድር ባሉ መንግሥታት ሁሉ ላይ አንተ ብቻ አምላክ ነህ፤ ሰማይንና ምድርንም ፈጥረሃል።
17
አቤቱ፣ እግዚአብሔር ሆይ፤ ጆሮህን አዘንብል፤ አድምጥም። እግዚአብሔር ሆይ፤ ዐይኖችህን ክፈት፤ ተመልከትም። ሰናክሬም ሕያው አምላክን ለመሳደብ የላከውን ቃል ስማ።
18
“ እግዚአብሔር ሆይ፤ በርግጥ የአሦር ነገሥታት እነዚህን ሕዝቦች፣ ምድራቸውንም ሁሉ ባድማ አድርገዋል።
19
አማልክታቸውን ወደ እሳት ጥለዋል፤ በሰው እጅ የተቀረጹ የድንጋይና የዕንጨት ምስሎች እንጂ አማልክት አልነበሩምና።
20
አሁንም፣ እግዚአብሔር አምላካችን ሆይ፤ የምድር መንግሥታት ሁሉ አንተ እግዚአብሔር ብቻ አምላክ እንደ ሆንህ ያውቁ ዘንድ፣ አቤቱ ከእጁ አድነን።”
21
ከዚህ በኋላ የአሞጽ ልጅ ኢሳይያስ እንዲህ የሚል መልእክት ወደ ሕዝቅያስ ላከ፤ “የእስራኤል አምላክ እግዚአብሔር እንዲህ ይላል፤ ስለ አሦር ንጉሥ፣ ስለ ሰናክሬም ወደ እኔ ጸልየሃልና፣
22
እግዚአብሔር በእርሱ ላይ የተናገረው ቃል ይህ ነው፤ “ድንግሊቱ የጽዮን ልጅ፣ ንቃሃለች፣ አፊዛብሃለች፤ የኢየሩሳሌም ልጅ፣ አንተ ስትሸሽ ራሷን ነቅንቃብሃለች።
23
የሰደብኸውና ያቃለልኸው ማንን ነው? ድምፅህንስ ከፍ ከፍ ያደረግኸው፣ ዐይንህን በትዕቢት ያነሣኸው በማን ላይ ነው? በእስራኤል ቅዱስ ላይ ነው እኮ!
24
በመልእክተኞችህ በኩል፣ በጌታ ላይ ብዙ የስድብ ቃል ተናገርህ፤ እንዲህም አልህ፤ ‘በሠረገሎቼ ብዛት፣ የተራሮችንም ከፍታ፣ የሊባኖስንም ጫፍ ወጥቻለሁ፤ ረጃጅም ዝግባዎችን፣ የተመረጡ ጥዶችን ቈርጫለሁ፤ እጅግ ወደራቁት ከፍታዎች፣ እጅግ ውብ ወደሆኑትም ደኖች ደርሻለሁ፤
25
በባዕድ ምድር ጕድጓዶችን ቈፈርሁ፤ ከዚያም ውሃ ጠጣሁ። የግብፅን ምንጮች ሁሉ፣ በእግሬ ረግጬ አደረቅሁ።’
26
“ይህን ቀድሞ እንደ ወሰንሁት፣ ጥንትም እንዳቀድሁት፣ አልሰማህምን? አሁን ደግሞ እንዲፈጸም አደረግሁት፤ አንተም የተመሸጉትን ከተሞች የድንጋይ ክምር አደረግሃቸው።
27
የሕዝቦቻቸው ኀይል ተሟጥጧል፤ ደንግጠዋል፤ ተዋርደዋልም፤ በሜዳ እንዳሉ ዕፀዋት፣ እንደ ለጋ ቡቃያ፣ በሰገነት ላይ እንደ በቀለ ሣር፣ በእንጭጩ ዋግ እንደ መታው ሆነዋል።
28
“ ‘እኔ ግን የት እንዳለህ፣ መምጣት መሄድህ ምን ጊዜ እንደ ሆነ፣ በእኔም ላይ እንዴት በቍጣ እንደምትነሣሣ ዐውቃለሁ።
29
በእኔ ላይ በቍጣ ስለ ተነሣሣህ፣ እብሪትህም ወደ ጆሮዬ ስለ ደረሰ፣ በአፍንጫህ ስናጌን፣ በአፍህ ልጓሜን አገባለሁ፤ በመጣህበትም መንገድ እንድትመለስ አደርግሃለሁ።’
30
“ሕዝቅያስ ሆይ፤ ይህ ምልክት ይሆንልሃል፤ “በዚህ ዓመት የገቦውን፣ በሚቀጥለው ዓመት ከገቦው የበቀለውን ትበላላችሁ፤ በሦስተኛው ዓመት ግን ትዘራላችሁ፤ ታጭዳላችሁ፤ ወይን ትተክላላችሁ፤ ፍሬውንም ትበላላችሁ።
31
እንደ ገናም የይሁዳ ቤት ቅሬታ፣ ሥሩን ወደ ታች ይሰድዳል፤ ከላይም ፍሬ ያፈራል፤
32
ቅሬታ የሆኑት ከኢየሩሳሌም፣ የተረፉትም ከጽዮን ተራራ ይመጣሉና፤ የሰራዊት ጌታ የእግዚአብሔር ቅናት ይህን ያደርጋል።
33
“ስለዚህ እግዚአብሔር ስለ አሦር ንጉሥ እንዲህ ይላል፤ “ወደዚች ከተማ አይገባም፤ ፍላጻ አይወረውርባትም፤ ጋሻ አንግቦ አይመጣባትም፤ በዐፈር ቍልልም አይከብባትም።
34
በመጣበት መንገድ ይመለሳል፤ ወደዚች ከተማም አይገባም” ይላል እግዚአብሔር ።
35
“ስለ ራሴና፣ ስለ አገልጋዬም ስለ ዳዊት፣ ይህችን ከተማ እጋርዳታለሁ፤ አድናታለሁም።”
36
ከዚያም የእግዚአብሔር መልአክ ወጣ፤ ከአሦራውያን ሰፈር አንድ መቶ ሰማንያ አምስት ሺሕ ሰው ገደለ፤ በሰፈር ያሉት ማለዳ ሲነሡ፤ ቦታው ሬሳ በሬሳ ነበር።
37
ስለዚህ የአሦር ንጉሥ ሰናክሬም አመለጠ፤ ወደ ነነዌም ተመልሶ በዚያ ተቀመጠ።
38
ሰናክሬም በአምላኩ በናሳራክ ቤተ ጣዖት በሚሰግድበት ጊዜ፣ ልጆቹ አድራሜሌክና ሳራሳር በሰይፍ ገደሉት፤ ከዚያም ወደ አራራት ምድር ኰበለሉ፤ ልጁም አስራዶን በምትኩ ነገሠ።
← Chapter 36
Chapter 38 →