bible
ra
🌐 Language
English
Español
Français
Deutsch
Português
Italiano
Nederlands
Русский
中文
日本語
한국어
العربية
Türkçe
Tiếng Việt
ไทย
Indonesia
All Languages
Home
/
Amharic
/
Amharic NASV (አዲሱ መደበኛ ትርጒም)
/
Exodus 18
Exodus 18
Amharic NASV (አዲሱ መደበኛ ትርጒም)
1
የምድያም ካህን የሙሴ ዐማት ዮቶር፣ እግዚአብሔር (ኤሎሂም) ለሙሴና ለሕዝቡ ለእስራኤል ያደረገላቸውን ሁሉ እንዲሁም እግዚአብሔር (ያህዌ) እስራኤልን ከግብፅ እንዴት እንዳወጣቸው ሰማ።
2
ሙሴ ሚስቱን ሲፓራን ከመለሳት በኋላ ዐማቱ ዮቶር እርሷንና ሁለት ወንድ ልጆቿን ተቀብሏቸው ነበር።
3
ሙሴ፣ “በባዕድ አገር መጻተኛ ነኝ” ለማለት የመጀመሪያ ልጁን ስም ጌርሳም አለው።
4
“የአባቴ አምላክ ረዳቴ ነው፤ ከፈርዖን ሰይፍ አድኖኛልና” ለማለት ደግሞ ሁለተኛውን ልጁን አልዓዛር አለው።
5
የሙሴ ዐማት ዮቶር ከሙሴ ወንድ ልጆችና ሚስት ጋር ሆኖ በምድረ በዳ ከእግዚአብሔር (ኤሎሂም) ተራራ አጠገብ ወደ ሰፈረበት ወደ ሙሴ መጣ።
6
ዮቶር፣ “እኔ ዐማትህ ዮቶር፣ ከሚስትህና ከሁለት ወንዶች ልጆቿ ጋር እየመጣን ነው” ሲል መልእክት ላከበት።
7
ስለዚህ ሙሴ ዐማቱን ሊቀበለው ወጣ፤ ዝቅ ብሎ እጅ በመንሣትም ሳመው፤ ከዚያም ሰላምታ ተለዋውጠው ወደ ድንኳኑ ገቡ።
8
ሙሴም እግዚአብሔር (ያህዌ) ለእስራኤል ሲል በፈርዖንና በግብፃውያን ላይ ያደረገውን ሁሉ፣ በመንገድም ላይ ስላጋጠማቸው መከራ ሁሉና እግዚአብሔርም (ያህዌ) እንዴት እንዳዳናቸው ለዐማቱ ነገረው።
9
ዮቶርም እግዚአብሔር (ያህዌ) እነርሱን ከግብፃውያን እጅ በመታደግ ለእስራኤል ያደረገውን በጎ ነገር ሁሉ በመስማቱ ተደሰተ።
10
እንዲህም አለ፤ “ከግብፃውያን እጅና ከፈርዖን ለታደጋችሁ፣ ከግብፃውያን እጅ ሕዝቡን ለታደገ ለእግዚአብሔር (ያህዌ) ምስጋና ይሁን”።
11
“ እግዚአብሔር (ያህዌ) ከአማልክት ሁሉ በላይ ኀያል እንደ ሆነ አሁን ዐወቅሁ፤ እስራኤልን በትዕቢት ይዘው በነበሩት ሁሉ ላይ ይህን አድርጓልና።”
12
ከዚያም የሙሴ ዐማት ዮቶር የሚቃጠል መሥዋዕትና ሌሎች መሥዋዕቶች ለእግዚአብሔር (ኤሎሂም) አቀረበ፤ አሮንም ከሙሴ ዐማት ጋር በእግዚአብሔር (ኤሎሂም) ፊት እንጀራ ለመብላት ከእስራኤል አለቆች ሁሉ ጋር መጣ።
13
በማግስቱም ሙሴ ሕዝቡን ለመዳኘት ተቀመጠ፤ እነርሱም በዙሪያው ከጧት እስከ ማታ ድረስ ቆሙ።
14
ዐማቱም ሙሴ ለሕዝቡ የሚያደርገውን ሁሉ ባየ ጊዜ፣ “ምን ማድረግህ ነው? እነዚህ ሁሉ ሰዎች ከጧት እስከ ማታ በዙሪያህ ቆመው ሳለ፣ ብቻህን በፍርድ ወንበር ላይ ለምን ትቀመጣለህ?” አለው።
15
ሙሴም እንዲህ ብሎ መለሰለት፤ “ምክንያቱም ሰዎቹ የእግዚአብሔርን (ኤሎሂም) ፈቃድ በመፈለግ ወደ እኔ ይመጣሉ።
16
ክርክር በኖራቸው ቍጥር ጕዳያቸው ወደ እኔ ይመጣል፤ ለግራና ለቀኙ የሚሆነውን እኔ ወስኜ የእግዚአብሔርን (ኤሎሂም) ሥርዐትና ሕጎች እነግራቸዋለሁ።”
17
የሙሴ ዐማት መልሶ እንዲህ አለው። “የምትሠራው መልካም አይደለም።
18
አንተና ወደ አንተ የሚመጡት እነዚህ ሰዎች የምታደርጉት ነገር ቢኖር ራሳችሁን ማድከም ነው፤ ሥራው ለአንተ ከባድ ሸክም ነው፤ ብቻህን ልትወጣው አትችልም።
19
ምክር እሰጥሃለሁና አሁን እኔን አድምጠኝ፤ እግዚአብሔር (ኤሎሂም) ከአንተ ጋር ይሁን። አንተ በእግዚአብሔር (ኤሎሂም) ፊት (የሕዝብ ተወካይ መሆን አለብህ)፤ ክርክራቸውን ወደ እርሱ ታቀርባለህ።
20
ሥርዐቶቹንና ሕጎቹን አስተምራቸው፤ እንዴት መኖር እንዳለባቸውና ምን መሥራት እንደሚገባቸው አሳያቸው።
21
ነገር ግን ችሎታ ያላቸውን ሰዎች ከሕዝቡ ሁሉ ምረጥ፤ እነዚህም ሰዎች እግዚአብሔርን (ኤሎሂም) የሚፈሩ፣ ታማኞችና በማታለል የሚገኘውን ጥቅም የሚጸየፉ ይሁኑ። የሺሕ፣ የመቶ፣ የአምሳ፣ የዐሥር፣ አለቃ አድርገህ ሹማቸው።
22
በማንኛውም ጊዜ ሕዝቡን ይዳኙ፤ ቀላሉን ነገር እነርሱ ይወስኑ፤ አስቸጋሪ የሆነውን ጕዳይ ሁሉ ግን ለአንተ እንዲያቀርቡ አድርግ፤ ሥራውን ስለሚያግዙህ ሸክምህ ይቃለላል።
23
አንተ ይህን ብታደርግና እግዚአብሔርም (ኤሎሂም) ይህንኑ ቢያዝህ፣ ድካምህን መቋቋም ትችላለህ፤ እነዚህም ሰዎች ሁሉ ረክተው ወደ ቤታቸው ይሄዳሉ።”
24
ሙሴ ዐማቱን ሰማ፤ ያለውንም ሁሉ ፈጸመ።
25
ከእስራኤል መካከል ችሎታ ያላቸውን ሰዎች መረጠና፤ የሕዝብ መሪዎች፣ በሺዎች፣ በመቶዎች፣ በአምሳዎች በዐሥሮች ላይም አለቆች አደረጋቸው።
26
ሁልጊዜም የሕዝብ ዳኞች ሆነው አገለገሉ፤ አስቸጋሪ ጕዳዮችን ወደ ሙሴ አመጡ፤ ቀላል የሆነውን ራሳቸው ወሰኑ።
27
ከዚያም ሙሴ ዐማቱን በጕዞው ሸኘው፤ ዮቶርም ወደ አገሩ ተመለሰ።
← Chapter 17
Chapter 19 →